Thursday, November 1, 2012

አከራዮቼ 1



እንደው መታደል ሆኖ ከኢትዮጵያዊ እናት ተፈጠርኩኝ እንጂ ወላጆቼ ፈርዶባቸው ፈረንጅ ቢሆኑ ኖሮ እድሜዬ ለአቅመ ሸክም በደረሰ በዚያ ወቅት (በ19 ዓመቴ ማለት ነው) “ሌላ ቤት ተከራይ አሊያም ኪራይ ክፈል” ይሉኝ ነበር፡፡ ያን ጊዜ ግን እኔ ራሴን መቻል ያሰኘኝ ወቅት ስለነበር እናቴን ሔጄ "ራሴን አሸክሚኝ" ስላት አንድ ቃል ነበር ከአፏ የወጣው “አትቅበጥ” የሚል፡፡ አዲስ ቦታ፣ አዲስ ሰው፣ አዲስ ነገር ሁሉ ደስ ይለኛል፡፡ አንድ ነገር ወይንም አንድ ቦታ ላይ ችክ ማለት አልችልበትም፡፡ ስልቹ ነገር ነኝ፡፡ የምሰራበት ቦታ ላይ ሁልጊዜ አዳዲስ ነገሮችን መፍጠር ካልቻልኩ ቀኑን መግፋት ያቅተኛል፡፡ ተደጋጋሚ(Routine) ነገሮችን እንደመፈፀም የሚያሳምመኝ ነገር እስካሁን የለም፡፡ ለነገሩ ስራ ላይ ብቻ ሳይሆን ቤት ኪራይ ላይም እንዲሁ ነኝ፡፡ ባለፉት በአስር አመታት ውስጥ እንኳን ስምንት ቤቶችን ለዋውጫለሁ፡፡ ኪራይ እስከሆነ ድረስ ምን አንድ ቦታ ላይ አስቸከለኝ?