Posts

Showing posts with the label Meles Zenawi

ዳግም ትንሳዔ???

Image
የጠቅላይ ሚኒስትራችንን ጤንነት በተመለከተ ባለፉትን አርባ አምስት ቀናት ይዘገቡ የነበሩ ዜናዎች እና ከወዲህ ወዲያ የተሰነዘሩት አስተያየቶች እርስበርሳቸው የተጣረሱ ከመሆናቸው ባሻገር የብዙ ለውጥ ፈላጊዎችን ደም ሞቅ ያደረገ ሁኔታ ሆኖ ተስተውሏል፡፡ ነፃ የመተንፈሻ ሚዲያ ያጣው የኢትዮጵያ ህዝብም በየፊናው ሆኖ የየራሱን ስሜትና ምኞት ባገኘው የማህበራዊ ድረ ገፅ ላይ መለጠፉን ተያይዞታል፡፡ አንዱ አዋቂ "ጠ/ሚሩ ከሞቱ 2 ሳምንት አለፋቸው" ሲል ሌላኛው አዋቂ ደግሞ "ንጉሳችን በድል አ/አ ገቡ" ይላል፡፡ አንደኛው የዜና አውታር "ጠ/ሚሩ ከጭንቅላት ጋር የተገናኘ ህመም ይዟቸዋል" ሲለን ሌላኛው ከመቅፅበት "የለም እሳቸውን ካልጋ ያስተዋወቀው የቆየ የሆድ ህመማቸው ነው" ይለናል፡፡ በተለይ ፌስቡክ እና ትዊተር ድረ ገፆች የተቻላቸውን ያህል የየሰውን ስሜት ሲያስተጋቡ ከረመዋል፡፡ ከአንዴም ሶስት ጊዜ ህልፈታቸው በደማቅ አራት ነጥቦች ታጅቦ ታውጇል፡፡ ያንኑ ያህል ግዜም ባይኔ በብረቱ አይቻቸዋለሁ በሚመስል ድፍረት "ሰውየው አዲስ አበባ ምኒልክ ቤ/መ ውስጥ ጋቢ ደረብ አድርገው ሶፋቸው ላይ ጋደም ብለው ሲ ኤን ኤን ከፍተው ዘ ኢኮኖሚስትን እያነበቡ አጃ ነገር እየጠጡ ነው" ያለም አልጠፋም፡፡ ይህ ሁሉ ሲሆን ግን እንደሰከረ ሰው ከመዘላበድ ውጪ አንድም የመንግስት አካል በግልፅ ስለጠቅላይ ሚኒስትሩ ጤንነት ማብራርያ መስጠት አልደፈሩም፡፡